ግልፅ
ደብዳቤ ለጠቅላይ
ሚ/ር መለስ ዜናዊ
ይህችን
የኔን አጭር ፅሁፍ ምን
አይነት ጊዜ ተርፎዎት
ሊያነቡ እንደሚችሉ አላውቅም::
ምክንያቱም እርስዎ በአሁኑ
ሰአት ባሰሯቸው በእነዚህ
የኢትዮጵያ ብርቅ ዜጎች፣
የነፃነት ጎህ ቀዳጆች
እና የቁርጥ ቀን ልጆች
በሆኑት የቅንጅት መሪዎች
ላይ ለማስፈረድ ነገር
እየተበተቡ እንደሆነ
በግልፅ የሚታወቅ በመሆኑ
ነው::
ይህ
ሁሉ መዳከር ደግሞ እርስዎም
ሆኑ አጋሮችዎ እውነተኛው
ፍርድ በፈጣሪ የሚሰጥ
እንጂ የሰው ፍርድ ከንቱ
መሆኑን ካለመረዳታችሁ
ሳቢያ የሚመነጭ መሰረታዊ ችግር ነው::
(ዳሩ በየትኛው ሐይማኖታችሁ!)
እርስዎ በአሁኑ
ሰአት በጣም ሰፊ በሆኑ
አራት መስቀለኛ መንገዶች
መሓል ላይ የመኪናዎችን
አካሄድ ለመምራት የቆሙ
ትራፊክ ተመስለው ይታዩኛል::
እናም እነዚህን መኪናዎች
በአግባቡ መምራትና ማስተናገድ
ባይችሉ፣ ወይም የርስዎ
ወዳጆች የያዙዋቸው መኪኖች
ወደበዙበት መንገድ ብቻ
በማየት ቅድሚያ እየሰጡ
የትራፊክ መጨናነቅ ቢፈጥሩ
(እየተፈጠረ እንዳለው
) ሁለት ዋነኛ ነገሮች
አይቀሬ ናቸው::
1= ሁሉም
ሊደርስበት ወዳለው ግብ
ለመሮጥ የራሱን መንገድ
እየመረጠ ጉዞውን ሲቀጥል
እርስዎ በፍፁም መምራት
የማይችሉበት ሁኔታ ውስጥ
ይሆኑና መሃል ላይ እንደግዑዝ
ሐውልት ቆመው ይቀራሉ::
እርስዎ ሊያስቀድሟቸው
ያሰቧቸው የወዳጆችዎ
መኪኖችም የርስዎን ዝም
ብሎ መቆም ሲያዩ ሌሎች
በመረጧቸው አማራጭ መንገዶች
ቀስ እያሉ በመግባት አዲስ
ጉዞ ይቀጥላሉ:: (በግልፅ
እየታየ እንዳለው)
2= ሌላውና
አደገኛው:- የተፈጠረው
የትራፊክ መጨናነቅ በሚያስከትለው
አደጋ የመጀመሪያ ተጠቂ
እርስዎ መሐል ላይ የተገተሩት
ትራፊክ ተብዬ ነዎት::
አቶ በረከት እና አቶ
አዲሱ ለገሰ የሚያሽከረክሯቸው
መኪኖች እንኳን ሳይቀሩ
በመጨረሻ ሰአት ከትርምሱ
ለመውጣት የራሳቸውን
መንገድ ይጠቀማሉ:: እርስዎን
ጭኖ እንኳን ለመሄድ የሚያቆሙበት
ቦታ አይኖራቸውም ወይም
አይፈልጉም «ሀ ራስን
ማዳን» ይሆንባቸውና::
ጠቅላይ
ሚ/ር ሆይ እስከአሁን
የሚቻልዎትን ሁሉ አድርገዋል
እያደረጉም ነው:: በዚህም
የኢትዮጵያን ሕዝብ ዝም
ያሰኙ መስሎዎት ይሆናል::
መቼም ግራ መጋባቱ ሕሊናዎትን
ደፍኖት እንጂ ብዙ ታሪክ
ያውቃሉ:: ከዛሬ መቶ አመት
በፊት በታሪክ ልውሰድዎትና
ባልሳሳት ዓፄ ምንሊክ
ይመስሉኛልሕዝቡ ግብር
ጨምሮ እንዲከፍል ትዕዛዝ
ቢያስተላልፉ ሕዝቡም
በንዴት ጮኸ፣ ይህንንም
ባለሟሎቻቸው ወጥተው
የሕዝቡን ቁጣ ቢነግሯቸው
እሳቸውም «እንግዲያው
አሁንም ጨምሩበት ያርፋል::»
ብለው ትዕዛዝ ሰጡ፣ አሁንም
ሕዝብ ለሁለተኛ ጊዜ ቁጣውን
ይበልጥ አሰማ:: ይሄም
መልዕክት በድጋሚ ቢደርሳቸው
አሁንም በትዕቢት «ለሶስተኛ
ጊዜ ጨምሩበት በደንብ
ይጩህ » ቢሉ ሕዝቡ ግን
ለሶስተኛው ጭማሪ ቁጣውን
ትቶ በልቡ እየመከረ ፀጥ
አለ:: ይበልጥ ጩኸት የጠበቁት
ዓፄ የፀጥታው መልስ ሲነገራቸው
« አይ አሁን ነው መፍራት!»
ብለው ማሻሻያዎችን ለመውስድ
ተገደዋል::
በዚያን
ዘመን እንኳ እንዲህ
ዓይነት ማስተዋል
ታይቷል: እርስዎ ግን
ከ 100 አመት በኋላ ዓለም
ሁሉ እየሰለጠነ
ባለበት ሰአት
ማስተዋል ተሳነዎት::እኔ
እንኳ በአቅራቢያዬ
በማውቀውና
በምከታተለው ሁኔታ
ልንገርዎት የኢትዮጵያ
ሕዝብ አልተኛም-
በፍፁም::
ክቡርነትዎ
« ለቀባሪው አረዱት»
ቢሆንብኝም ጥቂት
ነገሮችን ልጨምርና
ፅሁፌን ላብቃ::
በአለማችን ላይ
የተከሰቱትን የብዙ
አምባገነኖችን ታሪክ
እንተውና በጣም ጥቂት
የቅርብ ጊዜ
ትዝታዎችን እንይ::
እውነት
እንነጋገር ከተባለ
ኮለኔል መንግስቱ
በመጨረሻዋ ሰአት ላይ
እንኳ በሃገር
ሽማግሌዎች ለድርድር
እንዲቀርቡ ቢጠየቁ «ይህ የባልና
የሚስት የፀብ ጉዳይ
አይደለም» ብለው
መናገር የቻሉ መስሏቸው
ተሳለቁ፣ በኋላም
ውርደትን ተቀበሉ::
የላይቤርያው ቻርልስ
ቴይለር እንደዚያ
ተዋርደው
እንደመንደር ውስጥ
ሌባ እጃቸውን የኋሊት
ታስረው ወደ እስር
ቤት ሲወረወሩ ምን
እንደተሰማዎት
ባላውቅም መቼም
አንካካድም አሳምረው
አይተዋል::
በርግጥ
የሳዳም ሁሴንን ጉዳይ
እንዳላየ ቢሆኑ
ይሻልዎታል::
እርስዎም እዚያ ደረጃ
ላይ ለመድረስ ፉክክር
ላይ ካልሆኑ በቀር::
እንግዲህ
እነዚህ ሁሉም ነገር
ተሟልቶላቸው የነበሩ
መሪዎች ይህ ነገር
ከኋላቸው እንደሚመጣ
ቢያውቁ ኖሮ ያን ሁሉ
ደባ አይፈፅሙም
ነበር:: በርግጥ በኋላ
የሚሆነውን ማንም
አያውቅም ግን
አካሄድን አይቶ
መገመት ይቻላል:: ሰው
ደግሞ ካለፉ
ስህተቶችና ገጠመኞች
እየተማረ ይሄዳል
ይህን ካላደረገ ግን
መጀመሪያውኑ ስሙ
እንጂ በባህሪው ሰው
መሆኑ ጥያቄ ውስጥ
ይገባል::
እናም
ጠቅላይ ሚ/ር እርስዎ
አሁን ያኔ
እንዳፌዙባት 11ኛው
ሰአት ላይ ብቻ ሳይሆኑ
የመጨረሻዎቹ
ሴኮንዶች ላይ
ይገኛሉ፣
እያንዳንዷም ሴኮንድ
ነገሮችን ይበልጥ
የሚያወሳስቡበት
ሳይሆን ለመፍታት
ጥረት የሚያደርጉበት
ወሳኝ ሰአት ነውና
ልብ ሊሉ ይገባል::
ፈጣሪ
ዓምላክ መሃሪ ነውና የሚያስተውል
ልቦና ይስጥዎት::
ተሻለ ወ/ገብርኤል
( አርጋው - ስዊዘርላንድ)
|